Home

ድሕረ ገጽ ዜና ደብረ ጽዮን፤

“በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ስትቆም ከቅዱሳን መላእክት ጋር በገነት እንዳለህ ቁጠር ከወንድሞችህ ጋር አብረህ መፀለይህ የማይገባህ አድርገህ በማሰብ ራስህን አዋርድ ፡፡ወንድሞች እንዴት እንደቆሙ ወይም እንዴት እንደሚያዜሙ ለመመልከት ፊት እና ወደ ኋላ እንዳትገላመጥ በንቃት ቁም ፡፡ ይልቁንም ራስህን ዜማህንና ኃጢያቶችህን ብቻ ተመልከት፡፡”

ታላቁ የስነ መለኮት ሊቅ ቅዱስ ስምኦን


በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን - ርዕሰ አድባራት ለንደን ደብረ ጽዮን

ይህ ዜና ደብረ ጽዮን የሚለው የኢንተርኔት ላይ የመረጃ ምንጭ የተክፈተው በእንግሊዝ ሀገር በሎንደን ከተማ የዛሬ አርባ ዓመት በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ በብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ቡራኬ በእግዚያብሔር ፈቃድ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ አማንያን እምነቱን ጠብቆ እንዲኖር መንፈሳዊ አግልግሎት መስጠት እንዲቻል በተመሠረተችው ርዕሰ አድባራት ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ የተፈጠረውን ወቅታዊ ችግር በሚመለከት ለመላው ካህናት፣ ምዕመናንና ወጣት የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት እንዲሁም በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ ለምትኖሩ ለመላው ኢትዮያዊያን ወገኖቻችን ሁሉ ከሕገ ቤተክርስቲያን አኳያ ሕጋዊ፣ እውነተኛ፣ ተጨባጭ፣ ማስረጃዎችንና መረጃዎችን ለመስጠት ታስቦ የተከፈተ ነው።

በቤተክርስቲያን ውስጥ የተፈጠረው ችግር ሁለት ክፍሎች ናቸው።

1ኛ. ቤተ ክርስቲያናችን በቅዱስ ሲኖዶስ ሥር በቃለ አዋዲው የበላይ መመሪያ መሠረት በተጭማሪም ቤተክርስቲያኑ ከመገዛቱ አስቀደሞ ከ1984 ዓ.ም ጀምሮ በእንግሊዝ ሀገር በምግባረ ሰናይ ድርጂት(ቻሪቲ ኮሚሽን) አስተዳደር ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ የማይሸጥ የማይለወጥ ለሌላ ወገን ተላልፎ የማይሰጥ ማህበረ ካሀናቱና ምዕመናኑ በአንደነት በሚመርጣቸው አደራ ጠባቂዎች (የሰብካ ጉባዔ አስተዳደር አባላት) እንድትመራ የሚሉ ካህናት፣ ምዕመናንና ወጣት የሰንበት ትምህርት ቤት አባልትን ያካተተ፡

2ኛ. ጥቂት ግለሰቦች አብዛኛው በቤተሰባዊ ትስስር ያላቸው ክፍሎችና አሁን ነገሩ እየተባባሰ ከመጣ በኃላ ተቃዋሚ ፓለቲከኞችን ባካተተ መልኩ ቤተ ክርስቲያኑ ከቻሪቲ ኮሚሽን አስተዳደር አስወጥቶ በወለድ አግድ፣ ባንክ ለመበደር፣ ከሌሎች አትራፊ ድርጂቶች ጋር ሽርክና ለመግባት አመች በሆነ መልኩ ኃላፊነቱ በተወሰነ የግል ኩባንያ ካህናት የሌሉበት በሁለት ግለሰቦች የዴሬክተርነት የንብረት ባለቤትነት አስመዝግበው በግል ለመያዝ በሚፈልጉት መካከል የተፈጠረ ነው።

ከላይ በቁጥር (1ኛ) የተመለከተው ሕጋዊ የቤተክርስቲያን አስተዳደር እንደ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መረጃና እንደ ቤተክርስቲያነችን እምነት ቤተክርስቲያንን የመሰሠረታት እራሱ ኢየሱስ ከርስቶስ ነው። የቤተክርስቲያን እራስም እራሱ ክርስቶስ እንደመሆኑ መጠን ኤፌሶን 5፤23 አንድ ግዜ ከሱ ጋር ተዋህዳለች ። እኛ በውስጥዋ የምናመልክ ክርስቲያኖችም የክርስቶስ የአካል ክፈሎች ነን። ኤፌሶን 5፤30 ቤተ ክርስትያን ከንግድ ቤቶች ጋር ዝምደና በመፈጠር የጥሬ ገንዘብ አትራፊ ደርጂት አትሆንም።የእግዚያብሔር ቤት የጸሎት ቤት ናት። ማቴዎስ 21፤13 ዓላማና ተግባርዋ በቅዱስ ወንጌል መሰረት ስብከተ ወጌልን በማስፋት የአማኖችን ቁጥር ማብዛት ነው።

ካህናትም በሐዋርያት እግር ተተክተው በመንፈስ ቅዱስ ስም ምለው የተቀበሉትን ክህነት ጠብቀውና አክብረው የወንጌል ገበሬዎች በመሆን ወንጌልን በሕግ ቤትክርስቲያን መሠረት እያሰፋፉ ምዕመናንን የተሟላ መንፈሳዊ አገልግሎት እንዲያገኙ ማደረግ።ጢሞቴዎስ 5፤17 ቤተክርስቲያንን በቃለ አዋዲው መሠረት ከካህናት፣ ከምዕመናንና ከወጣት ሰንበት ተማሪዎች በተውጣጡ የሰባካ መንፈሳዊ ጉባዔ አስተዳደር አባላት ማስተዳደር ነው።ቃለ አዋዲ ምራፍ 3 አንቀጽ 7 ቁጥር 1 የቅዱስ ሲኖዶስና በየደረጃው ያሉ የኢትዮጵያ አርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የበላይ የአስተዳደር ክፍሎች ቃለ አዋዲውን ጠብቀው የሚሰጡትን ሃይማኖታዊ የአስተዳደር መመሪያ ጠብቆ ማስጠበቅ ነው።

በሌላ በኩል በቁጥር (2ኛ) የተጠቀሰው ከቤተ ክርስቲያናችን መመሪያና ውጭ በቤተ ክርስቲያኑን ሕንጻ ላይ የተመሰረተ በግል የንብረት ባለቤትነት ላይ ባተኮረ መልኩ ቤተ ክርስቲያኑን ኃላፊነቱ በተወሰነ የግል ኩባንያ በማስመዝገብ የተፈጠረው ችግር ከጊዜ ጊዜ እየተባባሰ መጥቶ በተለይም ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑን ወደ ግል ካንፓኒ በድብቅ ያስመዘገቡ ወገኖች ችግሩን እያጠናከሩና ከዚያም አልፈው ከፓለቲካ አጀንዳ ጋር በማያያዝ የአመጽ ተከታይ አብዝቶ ወደ ቤተ ክርስቲያን ዘልቆ በመግባት የክርስትና እና የቅዳሴ መንፈሳዊ አግልግሎት ሃይማኖታዊ ሥርዓቱን ጠብቆ እንዳይከናወን ሰላማዊ ሰልፍ በማድረግ ከፈተኛ የሆነ አመጽ በማካሄዳቸው ችግሩ በሕግ እስኪፈታ ድረስ ቤተ ክርስቲያኑ በግዳጅ ተዘግትዋል።

የግለሰቦቹ ዓላማ የቤተክርስቲያን ሀብትና ንብረት እኛ እናስተዳደራለን ካህናት ከመንፈሳዊ አገልግሎት ውጪ በየትኛውም አስተዳደር ሂደት ውስጥ እንዳይገቡ መገደብና በቃለ አዋዲው ሕግ፣ በውስጥ መተዳደሪያ ደንብ እና በቻሪቲ ኮሚሽን የሚያዘውን የቅዱስ ሲኖዶስ የበላይ መብት፣ ሃይማኖታዊ ኃላፊነትና ሥልጣን በመጣስ በግላቸው ለግለሰብን የግል የዞታንና ባለንብረትነትን የሚያረጋጥ ዋስትና ማስገኘት ነው።

በሕግ የተፈቀደ ሕግን አፈርሶ በቤተ ክርስቲያን የበላይ አስተዳደር ያለተፈቀደን፣ያለታወቀና ያልጸደቀ ሕግ ተግባራዊ ማደረግ አይቻልም። ቃለ አዋዲ ምራፈ 3 አንቀጽ 7 ቁጥር 1 ፍደል መ የቤተክርስቲያን ሕግ አዲስ ሕንጻ በተገዛ ወይም በተሰራ ቆጥር የግለሰቦችን ፈላጎት ለማሳካት ሲባል የሚፈርስ የሚሰረዘና የሚደለዝ አይደለም። ቤተ ከርስቲያን በክተማም ሆነ በገጠር ብትገኝ፤ በጭቃም ሆነ በአማረ የምነ በረድ ሕንጻ ብትሰራ፣ በስደትም ሆነ በሀገር ውስጥ ብትገኝ ቤተክርስቲያን አንዲት ናት። ሕጓና ሥራዓቷም አንድ ነው። ምዕመናኑም አንድ ናቸው። ቤተ ክርስቲያንም የሁሉ ክርስቲያኖች ናት ብለን እናምናለን።

ይህን ከላይ በቁጥር 1ኛ እና 2ኛ የተጠቀሱትን ሕገ ቤተክርስቲያን በመጠበቅና ከሕገ ቤተክርስቲያን ውጪ ለመሆን በሚደረግ ፍትጊያ ምክንያት የተፈጠረው ችግር በመቀራረብ በመውያየትና በሰላም እንዲፈታ ብዙ ተደክሟል። ቤተክርስቲያንና መንጋውን እንዲጠብቁ የተወከሉ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ሀገር አቁዋርጠው ባህር ተሻግረው በተደጋጋሚ በመምጣት ጉዳዮን በሕገ ቤተ ከርስቲያን ለመፍታት የተቻላቸውን ሁሉ አደረገዋል፣ ሆኖም ግለሰቦቹ በራሳቸው ፈላጎት ላይ የተመሠረተ ግለሰባዊ ፈላጎታቸን እስካልተፈጸመ ድረስ ቤተክርስቲያኑ አይከፈትም በማለት አመጻቸውን እያካሄዱ ይገኛሉ።

የተሳሳቱ መረጃዎን በማቅረብ የቤተክርስቲያኑ ባንክ በግል አደራሻቸው ለማዛወር ያደረጉት ሙከራ፣ የቻሪቲ ኮሚሽንን ሕጋዊ የግል ባለቤት መስሎ በመቅረብ ለማሳስት የሚደረገው ከፈተኛ ጥረት ፣ ካህናትን መደብደብ፣ ስም ማጥፋት እና ቤተ ክርስቲያኑን ያለ ማህብረ ካህናቱና ምእመናን ፋቃድና ውሳኔ በግል የዞታ ኃላፊነቱ በተወሰነ የግል ኩባንያ ስም ማስመዝገብ ፣ እነዚህ ሁሉ ተግባራት የሚከናወኑት የቤተክርስቲያን ሕንጻ በባለቤትነት ለመቀማት የሚደረግ እንቢተኝነት ነው።

ምክረ ካህንን የማይቀበሉ ነገር ግን ምዕመናንን በመከፋፈል፣ በመለያየትና የተሳሳተ መረጃ በመስጠት እርስ በራስቸው መበታተን በየጊዜው ለጸብና ለአንባጓሮ በመጋበዝ ለተመልካች እጂግ በጣም አሳፋሪ በሆነና የማህበረሰባችን ገጽታ በሚያበላሽ ሁኔታ ያደረጉት አስከፊ ተግባር በየመረጃ ምንጩ ተበትኖ የምናየው አሰቃቂ ሁኔታ ሁሉ ከሕንጻ ቤተ ክርስቲያን የባለቤትነት ጥያቄ የመነጨ ነው። «መለያይት የሚያመጣን ሰው አንድ ጊዜ ወይም ሁለት ጊዜ ከመከርከው በኃላ ከርሱ እራቅ» ፊሊሞና 3፤10

በመሆኑም የዚህ ድህረ ገጽ ዓላማ በርዕሰ አድባራት ሎንደን ደብረ ጽዮን ቅደስት ማርያም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ከርስቲያን ሕንጻ የባለቤትነት ጥያቄ ላይ ያነጣጠረ አመጽ የሃይማኖታችን እንዳናመልክ ከመከልከሉንና ቤተክርስቲያናችን አስገድዶ ከማዘጋቱም አልፎ በስደት የምንገኘውን የኢትዮጵያዊነት ገጽታና ማህበራዊ ግኑኝነታችን ሁሉ እያበላሸ መሆኑን ማጋለጥና ሕገ ቤተክርስቲያን እንዲከበር ለሁሉም የቤተ ክርስቲያናችን ተክተዮች ካህናትና ምዕመናን ኢትዮጵያዊያን በሙሉ ሕጋዊ፣ ተማኝነትና በማሰረጃ የተደገፈ መርጃውችን ማሰተላለፍ፣ ትምህርተ ሃይማኖትን፣ሕገ ቤተክርስቲያንና ከቤተክርስቲያናችን ጋር ተያይዞ የመጣውን ሀገር አቀፋዊ ታሪክ ማስተማር ነው።

በተጨማሪም «……ሰው ሁሉ ሐሰተኛ ቢሆን እግዚአብሔር እውነተኛ ነው።» ሮሜ 3፤4 እውነተኛውን የግዚአብሔርን ሕግ ተከትለን ከሐሰት ይልቅ በእውነትና ለመንፈሳዊ ተግባር፣ ለእርቅና ለስምምነት፣ በሰለጠነ መልኩ ለመወያየትና ለመቀራረብ በሕገ ቤተክርስቲያን ለመመራት ዘግጁነት ካላቸው የግል ጥቅመኝነት፣ጠባብነትና ትምህክተኝነት ከማያጠቃቸው ምዕመናን ጋር በጋራ ጉዳያች ላይ ለመምክርና ውይይት ለማደረግ ብሎም ቤተክርስቲያናችን ከፈተን በሰላም ለመገልገልና ለማገስገልገል ምንግዜም ለሰላም ለሚደረግ ማንኛውም ዝግጂት ሁሉ የዜና ደብረ ጽዮን ድህረ ገጽ ተቀዳሚ ዓላማ መሆኑን በታላቅ መንፈሳዊ አክብሮት እንገልጻለን።

እግዚአብሔር ቤተክርስቲያናችን በአንደነት ሕዝባችን በስምምነት ይጠብቅልን!

ዜና ደብረ ጽዮን፤

ጥቅምት 2006 ዓመተ ምህረት፤